08/01/2026
ካነበብኩት
……እንዴት ነው ነገሩ፤ አንድን ሥራ ሁለቴ የሠራሁበት? የምን አዙሪት ነው?'' አለ በመደነቅ። አዲስ ፍለጋ፣ አዲስ እንቆቅልሽ የመሰለው አሮጌ ሆነበት። በእውነቱ ማንን እየጠየቀ እንደሆነ እንኳን ግልጽ አለነበረም። በመካከላቸው ዝምታ ሰፈነ። አባ መዝገበ ሥላሴ ቆይተው፡, "አየህ ኃይለ ጊዮርጊስ! ሕይወት አዙሪት ናት። ረጅም ርቀት የተጓዝክ ቢመስልህ የምትጨርሰው ከጀመርክበት ነው" ራቁትክን ትወለዳለህ እርቃንህን ወደ መቃብር ትወርዳለህ። በጥርስ አልባው ድድህ እየጋጥክ ትጀምራለህ፤ ጥርሱን ባረገፈው ድድህ እያልጎጠጎጥክ ትጨርሳለህ። የሕይወትን ትግል እየዳህ ትጀምራለህ፤ አጎንብሰህ ትጨርሳለህ። ዘመንም ተምኔታዊ ነው። መስከረም ጥቅምት ብለ ያስጀምርህና መስከረም ብሎ ይመጣብሃል። ሰኞ ማክሰኞ ብለህ ተጉዘህ እንደገና ሰኞ ትላለህ። ሕይወት አዙሪት ናት! መጀመሪያህ መጨረሻህ ነው። የጀመርክበትን አትርሳ፤ መጨረሻህ ነውና። የጀመርክበትን አትናቀው፣ ትጨርስበታለህና። ተራ ሰው ሆነህ ትጀምራለሁ፡ ተምረህ ዕወቀት ብትጨምር፣ ነግደህ ሀብት ብታገኝ፣ ተሹመህ በሕዝብ ላይ ብትሰለጥን፣ ክቡረ ክቡራን ሆነህ የወርቅ ካባ ብትለብስ የምትጨርሰው እንደ ተራ ሰው አፈር ለብሰህ ነው።" ሲሳይ ከአድናቆት በስተቀር የሚጠይቅበትም፣ ሐሳብ የሚያቀርብበትም አቅም አልነበረውምና ዝም ብሎ እያዳመጣቸው ነበር።
ቀጠሉ ኣባ፡- “ልብ በል! ባለማወቅ ትጀምራለህ፤ በመዘንጋት ትጨርሳለህ፡ ዕውቀት አላመጣህምና ዕውቀትም ይዘህ አትሄድም። በለቅሶ ትጀምራለህ፤ በጭንቅ ትጨርሳለህ። በሰው እቅፍ ትጀምራለህ በሰው ሽክም ትጨርሳለህ። ልደትህ ከሞትህ በምን ይለያል? ሞትሀስ ከልደትህ በምን ይከፋል? ሕይወት መጨረሻዋና መጀመሪያዋ አንድ ነው። በዚህ የተነሣ ጠቢቡ እንዳለው ሁሉም የከንቱ ከንቱ ነው፤ ከፀሐይ በታች አዲስ ነገር የለም። ልብ በል! የዓለም ከንቱነት ግን ውበቷ ነው። ዓለም አዲስ ነገር ቢኖራት እኛን እንዴት በጸጸተን፤ ሞት የእውነት መጨረሻ ቢሆን እንዴት በቆጨን" አሉና “ርቀህ የሄድክ ቢመስልህም ትልቅ ክብ ሠርተህ ተመልሰህ እዚህ ትመጣለህ። ዋናውን ተግባርክን ግን እስካሁን አልጀመርከውም" አሉት።ሲሳይ የተረዳቸው አይመስልም። እርሱ ራሱ በጥልቅ መደነቅ ወስጥ ነበርና።……
መርበብት ፡ ዶ/ር ዓለማየሁ ዋሴ