17/03/2026
የወንድማችንን የመምህር ዘላለም ወንድሙን ነፍሰ ወደ ዘላለም ዕረፍቷ ሄዳለች ከቅዱሳኑ ጋር ትኖራለች መንግሰተ ሰማያትም የእርሷ ናትና ክብር ለድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርሰቶሰ ይሁን አሜን ።
እንደ ምስኪን ኖሮ እንደ ንጉስ ተሸኘ
በታሪክ ተደርጎ በማያውቅ መልኩ እነሆ ነጭ በነጭ ተለብሶላት የተሸኘች ነፍስ።መስቀል አደባባይ በእንባ ጎርፍ ታጠበ።ብጹአን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ቆሞሳት፣መነኮሳት፣ ካህናት፣ መዘምራን ፣ምእመመናን፣ነድያን ሁሉም እያነቡ ሸኙት።
መምህር ዘላለም ዝቅታን ሳያውቃት ከፍ እንዳለ ኖሮ በክብር ወደ አምላኩ ወደ አምላካችን ተሸኘ•••
ብቻውን አንድ ደብር፣ብቻውን አንድ ገዳም፣ብቻውን አንድ ቤተመጻህፍት ነበረ...ዕዩኝ ያላለ ትሁት፣ ስሙኝ ያላለ ምስጉን፣ቃላት እንደታናሽ ወንድሙ የታዘዘሉት፥የቀደሙ አባቶችን አንደበት የተላበሰ፣የማናችንም ዕዳ የሌለበት...
እንደምንወደው ሳንነግረው ሄደ፣ለሱ ያለንን አክብሮት ሳንገልጽለት የማእረግ ስም ሳይወጣለት መምህር/ዲያቆን ዘላለም እንደተባለ አረፈ።
እሱ ማስተማር ሲጀምር እንኩዋን ሰው የዛፍ ቅጥሎች እንኩዋን ማንሾካሾክ ያቆሙ ነበር። ደግነትን ያልጀመረ፣ትህትናን ያላስመሰለ፣ቅንንነትን ያልሞከረ የለም።
ጀምረው የጨረሱ ግን ጥቂቶች ናቸው።እነዚህን ሁሉ ግን መምህር ዘላለም አጣምሮ ኖረ።እንዴ ቻለው?እንዴትስ አወቀበት? እንዴትስ ዲያብሎስን ድል ነሳው?እንዴትስ ከገንዘብ ፍቅር፣ከጭብጨባ ብዛት፣ከሚድያን ጋጋታ ተደብቆ ኖረ?... አብሮን እያለ የማናየው ጻድቅ በመካከላችን እየተመላለሰ የተሰወረብን ባህታዊ...እሕሕሕ
የቤተክርስቲያን የልቧ ማረፊያ አረፈ:: መምህር ወመገስጽ ስሙ በክፉ የማይነሳ ፣ እዚህ አየነው ፣ ይህን ተናገረ በሚል የልዩነት ርዕስ ሆኖ የማያውቅ ሙሉ ሰው ፣ እግዚአብሔርን የሚፈራ ፣ ለምእመናን አንድነትና ለነፍሳቸው መዳን የሚጨነቅ ፣ በከተማ በገጠር ፣ በሀገር ቤት በውጭ በእኩል ዝግጅት ለወንጌል ሲተጋ የኖረ አገልጋይ ነበር::
እንኳን ሰው የቆመባት ዐውደ ምሕረት፣ የጨበጣት ማይክ አፍ አውጥታ የምትመሰክርለት የተግባር ሰው ነበር:: የቆመባት ዐውደ ምሕረት እነ መምሕር ዘላለም ወንድሙ ቆመውባት ነበር ተብሎ የሚመሰክርለት የመምህራን ምሣሌያችው እርሱ ነበር::
ከ250 በላይ ሕጻናትን አሳዳጊ፣ የአገልጋዮች ሕብረትን ፣ የሰራተኛ ጉባዔያትን እና ጊቢ ጉባዔያትን መስርቶና አስፍቶ ለብዙ ነፍሳት መዳን ምክንያት የሆነ ሐዋርያ ነበር:: ይሄንን እናገራለሁ :- የሰበከውን ኖሮታል ፤ የተናገረውን ፈጽሞታል ፤ የማንም ዕዳ የለበትም ፤ አገልግሎቱ የሠመረ ነበረ ፤ሰው ታንጾበታል፤ እግዚአብሔር ከብሮበታል::
በቤተክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ስማቸው በወርቅ ቀለም የሚጻፍ አገልጋዮች አሉ። እነዚህ አገልጋዮች የሐዋርያትን ፈለግ ተከትለው፣ የራሳቸውን ምቾትና መብት ለወንጌል መስፋፋት አሳልፈው የሰጡ ናቸው። መምህር ዘለዓለም ወንድሙ የዚህ ሕያው ምስክር ነበረ።
በዚች አለም በዚህም ዘመን የሚሰብኩትን መኖርም ቀላል አይደለም፤ ሞገዱና ወጥመዱ የበዛ ነውና።መምህር ዘለዓለም ወንድሙ ግን ሃይማኖቱን በርቱዕነት ለረዘሙ ዓመታት የአንደበት ወለምታ እንኳ ሳይኖርበት አስተምረዋል።
ሕይወቱን ያለ ነቀፋ አኑረዋል።ኃያሉን የመምህራን ፈተና ፍቅረ ንዋይን እስከ ፍጻሜያው ድል ነስቶታል። የምናዝነው እኛ ስለጎደለብን ነው:: የምናለቅሰው አባት መምህርና ወንድም ስላጣን ነው:: በአንጻሩ የምንጽናናው ሲያገለግለው ወደኖረው አምላክ በክብር ስለሄደ ነው:: የአገልግሎትህ በረከት ትድረሰን!
የእናታችን ቅድስት ቤተክርስቲያንን እንዲሁም መድረኳን አክብሮ አስከብሮ ያለፈ መምህራችን ነበር...እናት ኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ቅድስት ቤተክርስቲያን በዚህ ጊዜ ትልቅ ድምጿን ተከራካሪዋን የብርሃን ምሰሶዋን አጥታለች..አምነን የምንቀበለው ነጩ እውነታ ይኼን ነው...ጽናቱን ይስጠን!!
መምህሬ ሆይ...የሰማይ መላእክት በዝማሬ በምስጋና ይቀበሉህ... ስላሴ በእጃቸው ያኑሩህ ለእናትህ ለቤተሰብችህ ለአገልጋይ ጓደኞችህ ለመላው ህዝበ ክርስቲያን መጽናናትን ያድልልን ለቤተ ክርስቲያንም ተተኪ አያሳጣት...
በል እንግዲህ አንተ የጭብጨባ ብል ያልበላህ፣ የውዳሴ ነቀዝ ያላበላሸህ ድንቅ አገልጋይ የዐውደ ምሕረታችን ኮከብ ፣ዘይትህ ከማሰሮህ ሳይጎድል እንደበራህ ይኖርክ.... የሸለቆው ሐዋርያ ዘለዓለም ሆይ ወደ ዘለዓለሙ ቤትህ በሰላም ግባልን!
በሰላም ዕረፍ መምህራችን፣ አባታችን፣ ወንድማችን
Via፦Zelalem Tsegaye
ግዮን ማለዳ