29/05/2026
©
ቀን: ግንቦት 18 ቀን 2018 ዓ.ም (May 26, 2026)
ለክቡር የኢፌድሪ ጠቅላይ ሚኒስትር
አድራሻ: አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
ጉዳዩ: የብ/ጄኔራል አሸናፊ ገ/ፃዲቅን ብሄራዊ የጀግንነት ታሪክ ለማስታወስ እና ጥሪ ለማቅረብ የተዘጋጀ ልዩ የድጋፍ ደብዳቤ
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር፤
ለሀገራችን እድገት እና ደህንነት ለምታደርጉት ከፍተኛ አመራር ያለኝን ታላቅ አክብሮት እየገለጽኩ ፣ የቀድሞው የኢትዮጵያ አየር ኃይል እውቅና ያተረፉ ድንቅ ተዋጊ አብራሪ የሆኑትን የብ/ጄኔራል አሸናፊ ገ/ፃዲቅን ተአምራዊና ታሪካዊ የጀግንነት ውለታ በመጥቀስ፣ በመንግሥት ደረጃ ተገቢው ብሄራዊ እውቅና፣ መታሰቢያ እና የክብር ጥሪ እንዲደረግላቸው ይህንን የድጋፍ ደብዳቤ በታላቅ ኩራት አቀርባለሁ።
ብ/ጄነራል አሸናፊ ገ/ፃዲቅ የውጊያ ጄት (F-5 ተዋጊ አውሮፕላን) እየበረሩ ሳለ በአውሮፕላኑ የፊት ለፊት መደገፊያ እግር (Nose Gear) ሳይወርድ በመቅረቱ ምክንያት ያጋጠማቸውን ከፍተኛ የቴክኒክ ብልሽት እና የተደቀነውን እጅግ አደገኛ ሁኔታ በከፍተኛ ጥበብና ጀግንነት በመወጣት በኢትዮጵያ አቪዬሽን ታሪክ ውስጥ የማይረሳ ደማቅ ታሪክ አስመዝግበዋል።
በወቅቱ ከነበረው የአቪዬሽን መመሪያ አንጻር ራሳቸውን በፓራሹት አስወንጭፈው (Eject አድርገው) ሕይወታቸውን ማዳን የሚችሉበት የተፈቀደ አሰራር ቢኖርም ፣ እሳቸው ግን የሀገር ሀብት የሆነውን ውድ ተዋጊ አውሮፕላን ላለማጣት እና አውሮፕላኑን ያለምንም ቁጥጥር ቢለቁት በድሬዳዋ ከተማ ሰላማዊ ሰዎች ላይ ሊያደርስ የሚችለውን የህይወትና የንብረት እልቂት ለማስቀረት ሲሉ የገዛ ሕይወታቸውን ለአደጋ አጋልጠው አውሮፕላኑን ለማሳረፍ ወስነዋል።
በወቅቱ የድሬዳዋ አየር ማረፊያ የደህንነት ሰራተኞች በማኮብኮቢያው ላይ አረፋ (Foam) ቢረጩም፣ ማረፉ ግን አሁንም እጅግ አስፈሪና አደገኛ ነበር ፤ ሆኖም ብ/ጄነራል አሸናፊ አውሮፕላኑን በጣም በተረጋጋ ሁኔታ በማብረር የኋላ መጋለቢያ እግሮቹ (Main Gears) ብቻ መሬት እንዲነኩ ካደረጉ በኋላ፣ ፍጥነቱ እየቀነሰ በሄደ ቁጥር የፊቱ ክፍል መሬት ደርሶ እንዳይጋይና እሳት እንዳይነሳ የቁጥጥር ዘንጉን (Stick) ወደ ኋላ በመሳብ አፍንጫውን በአየር ላይ አንሳፈው አቆይተውታል። በመጨረሻም አውሮፕላኑ ፍጥነቱን ጨርሶ ሊቆም ጥቂት ሜትሮች ሲቀሩት ብቻ አፍንጫው መሬት እንዲነካ በማድረግ፣ ያለምንም እሳት አደጋ እና ያለ ምንም የሰው ህይወት ጉዳት አውሮፕላኑን በሰላም ማሳረፍ የቻሉ ሲሆን፣ ይህ አስደናቂ የመብረር ብቃት፣ የጸና ዲሲፕሊን እና ለሀገር ንብረት የነበራቸው ተቆርቋሪነት አውሮፕላኑ በወቅቱ ቀላል ጥገና ተደርጎለት ድጋሚ ለበረራ እንዲበቃ አስችሏል።
በመሆኑም ይህንን የመሰለ ለሀገርና ለወገን በራስ ህይወት የመጨከን ታላቅ የጀግንነት ምሳሌነትን ለትውልድ ማስተማሪያ እንዲሆን በታሪክ መዝገብ ጎልቶ እንዲቀመጥ፣ ለጄኔራሉ ብሄራዊ የክብር ጥሪና ተገቢው እውቅና እንዲሰጣቸው ክቡርነትዎ አስፈላጊውን መመሪያ ይሰጡ ዘንድ በአክብሮት እጠይቃለሁ።
ከታላቅ አክብሮት ጋር
ETAF_GlobalNetwork
www.formerethiopianairforce.com