04/04/2020
Share! Share! Share!
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ
ርእሰ ባሕታውያን ሊቀ አእላፍ ቆሞስ አባ ዮሐንስ ተስፋ ማርያም ከኢትዮጵያ ውጭ በተለያዩ ሀገራት ከሚኖሩ፣ በጸሎታቸው ከተለያዩ በሽታዎች ከተፈወሱ፣ ከሰይጣን ማሰሪያ ከተፈቱ፣ በረከት ካገኙና ‹‹ትጋት የአባ ዮሐንስ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎች›› በሚል በአንድነት በማኅበር ከተሰባሰቡ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸው ጋር በመሆን በተለያዩ ጊዜያት የበጎ አድራጎት ሥራዎችን እየሠሩ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡ አሁንም በእንባ፣ በጸሎት እግዚአብሔርን ከመለመንና ሕዝቡ ከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ከማስተማር ጋር በመላው ዓለም ላይ የተከሰተውንና ምድራችን እያስጨነቀ ያለውን የኮሮና ቫይረስ ለመከላከል ድጋፍ እንዲያደርጉ በተጠየቁት መሰረት ለአማራ ክልል በሽታውን ለመከላከል የሚውልና ለጎዳና ተዳዳሪዎች ድጋፍ የሚሆን 1,685,000 (አንድ ሚሊየን ስድስት መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ) ብር ድጋፍ አድርገዋል፡፡ ይህም ለአማራ ክልል ጤና ቢሮ ለሕክምና እቃዎች መግዣና ለጎዳና ተዳዳሪዎች ድጋፍ የሚሆን 1,000,000 (አንድ ሚሊየን) ብር፣ እንዲሁም የደቡብ ጎንደር ዞን ጤና ጥበቃ መምሪያ በአጠቃላይ በዞኑ ውስጥ ለሚገኙ ለሁሉም ወረዳዎች ለሕክምና ቁሳቁስ መግዣና ለጎዳና ተዳዳሪዎች ድጋፍ የሚሆን 585,000 (አምስት መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ) ብር ድጋፍ ያድርጉልን ብሎ በጠየቀው መሰረት 585,000 (አምስት መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ) ብር ድጋፍ አድርገዋል፡፡ በዞኑ ውስጥ ላሉ ሁሉም ወረዳዎች በዞኑ ጤና መምሪያ በኩል ከተደረገው ድጋፍ ሌላ ደራ ወረዳ ተጨማሪ የ100,000 ብር እርዳታ ያሥፈልገናል ብለው በመጠየቃቸው የ100,000 (አንድ መቶ ሺህ) ብር ድጋፍ ተደርገላቸዋል፡፡ እንዲሁም በዚሁ በደራ ወረዳ ከአራት መቶ በላይ የሚሆኑ አመራሮች ለአምስት ቀናት ላደረጉት ስብሰባ ድጋፍ በጠየቁት መሰረት አባታችን አባ ዮሐንስ ተስፋ ማርያም በስብሰባው መክፈቻና መዝጊያ ቀናት በመገኘት ስለ ልማት፣ ስለ ጸጥታና ስለጤና አስደሳች የሆነ ትምህርት ሰጥተው የጠየቁትን 123,800 (አንድ መቶ ሃያ ሦስት ሺህ ስምንት መቶ) ብር ድጋፍ ያደረጉላቸው ሲሆን በአጠቃላይ ከ1,808,000 (አንድ ሚሊየን ስምንት መቶ ስምንት ሺህ) ብር በላይ ድጋፍ አድርገዋል፡፡ አባታችን አባ ዮሐንስ ተስፋ ማርያም ከዚህም በፊት ከትጋት የአባ ዮሐንስ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎች ማኅበር ጋር በመሆን በ2011 ዓ.ም በሰሜን ጎንደር ለተፈናቀሉ ወገኖች የ1,000,000 (አንድ ሚሊየን) ብርና የ300 ኩንታል እህል ድጋፍ ማድረጋቸውና በአንበሳሜ ከተማ ዘመናዊ ትምህርት ቤት ሠርተው ማስረከባቸው አይዘነጋም፡፡ እንግዲህ፡- ብርሃንን ሠራሁ፥ ጨለማውንም ፈጠርሁ ደኅንነትን እሠራለሁ፥ ክፋትንም እፈጥራለሁ፤ እነዚህን ሁሉ ያደረግሁ እግዚአብሔር እኔ ነኝ። ኢሳ. 45÷7 ተብሎ እንደተጻፈ በቸርነቱ ሰላምንና ጤናችንን የሚሰጠንም ደግሞም ስናጠፋ የሚገስጸንም እሱ አምላካችን እግዚአብሔር ስለሆነ በሰው ልጆች ላይ እየደረሰ ያለውን ክፉ መቅሰፍት በመሐሪነቱ ያስወግድልን፤ በይቅርታው ይጎብኘን፡፡